ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን የምንሸመድድባቸው ዐሥር ምክንያቶች

የመጽሐፍ ቅዱስ ረጃጅም ክፍሎችን ብቻ ሳይሆን፣ ሙሉ አንድ መጽሐፍ ሳይቀር በቃላችሁ መያዝ ትችላላችሁ። ከባድ የጭንቅላት ጉዳት አልያም ስትሮክ ወይም ሌላ ዐይነት ጉዳት ካለባቸው ጥቂት የማኅበረ ሰቡ ክፍል ካልተመደባችሁ በቀር ይህን ማድረግ ትችላላችሁ። ልታደርጉትም ደግሞ ይገባል። ይሁን እንጂ ይህን ማድረግ ያለባችሁ ለምንድን ነው?

  1.  የማስታወስ አቅማችሁ ዝቅተኛ ስለ ሆነ

የማስታወስ አቅሜ ዝቅተኛ ስለ ሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን መሸምደድ አልችልም አትበሉ። እንዲያውም መሸምደድ ያለባችሁ በዚህ ምክንያት ነው። እኔም የማስታወስ ብቃቴ ደካማ ነው። እውነቴን ነው ምላችሁ፤ የማስታወስ አቅሜ ከብዙ ሰዎች የወረደ እንደ ሆነ አስባለሁ። የማውቃቸውን እና በተደጋጋሚ የማገኛቸውን ሰዎች ስም እረሳለሁ። እጅግ ወሳኝ የሆኑ ነገሮችን ለረጅም ጊዜ እንዲቀመጥ የማደርገው ደካማውን አእምሮዬን አስጨንቄ ነው። ይህንንም የማደርገው ነገሮችን በጊዜ ውስጥ በየዕለቱ በመደጋገም ወይም በመሸምደድ ነው። ቀላል ስልት ቢኖራችሁ እና የተወሰነ ጥረት ብታደርጉ ልታሳኩት የምትችሉት ነገር ያስደንቃችሁ ነበር። አምስት የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ሸምድጄ የጨረስኩ ሲሆን አሁን ስድስተኛዬን በመሸምደድ ላይ እገኛለሁ። ይህም ደግሞ እኔ ደካማ የማስታወስ አቅም ስላለኝ ነው።

  1.  አእምሯችሁን መመገብ ስላለባችሁ ነው

ፊልጵስዩስ 4፥8 እውነት የሆነውን ሁሉ፣ ክቡር የሆነውን ሁሉ፣ ትክክል የሆነውን ሁሉ፣ ንጹሕ የሆነውን ሁሉ፣ ተወዳጅ የሆነውን ሁሉ፣ መልካም የሆነውን ሁሉ እንድናስብ ይነግረናል። ይሁን እንጂ እንዲህ ያሉትን ነገሮች ካላስታወስናቸው ይህን እንዴት ልናደርግ እንችላለን? ጠቅለል ያሉ አዎንታዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ጽንሰ ሐሳቦች ብዙም ጠቃሚ አይደሉም። ለብቻችን ሆነን ከተስፋ መቁረጥ ወይም ንዴት ወይም ምኞት ወይም ፍርሀት ጋር ትግል ስንገጥም፣ ከትውስታችን ልንመዛቸው የምንችላቸው ውስን ሁኔታ ላይ ያተኮሩ “የከበሩ ታላላቅ የተስፋ ቃሎች” ያስፈልጉናል (2 ጴጥሮስ 1፥4)።

  1.  መጽሐፍ ቅዱስን በቀላሉ ልታገኙ ስለምትችሉ ነው

አንድን ነገር በቀላሉ ማግኘት እየቻልን ችላ ማለታችን ግር የሚል ነገር ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ሁልጊዜ በጠረጴዛችን ላይ፣ በስልካችን እና ኮምፒዩተራችን ላይ ካለ ከፍተን የተወሰኑ ክፍሎችን ልናነብብ፣ አንዳንዴም ቁልፍ ቃላትን በመጠቀም ሐሳቦችን ልንፈልግ እንችላለን። ይሁን እንጂ፣ ውስጣችን እንዲቀር ምንም ዐይነት ሸክም አይሰማንም። ይህንን ሽንገላ ልንዋጋው የምንችልበት አንደኛው መንገድ መጽሐፍ ቅዱስን በመሸምደድ ነው።

  1.  ኢንተርኔት ስላላችሁ ነው

በሚያሳዝን ሁኔታ፣ እንዴት ማንበብ እንደሌለብን ኢንተርኔት እያስተማረን ነው። መረጃ አሳሾች እየሆንን ነው። በፍጥነት እናስሳለን፤ ግን ብዙም አናብላላም። ጥልቅ ለሆኑና በሚገባ ለተብራሩ ጽሑፎች ትዕግሥት እያጣን ነው። ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን መሸምደድ ትርጉሙ ምን እንደ ሆነ እና ከሕይወታችን ጋር እንዴት ልናዛምደው እንደምንችል እንድናስብ ያስገድደናል።

  1.   መጽሐፍ ቅዱስን እንደሚገባ እናውቀዋለን ብላችሁ በምታስቡት ልክ ስለማታውቁት ነው

ለረጅም ጊዜ ከምታውቋቸው ወዳጆቻችሁ ጋር እያወራችሁ ከዚህ በፊት የማታውቁት ገጽታ እንዳላቸው ልብ እንድትሉ፣ እንዲሁም የበለጠ እንደ ተረዳችኋቸው እና እንደ ቀረባችኋቸው እንዲሰማችሁ ያደረገ ውይይት ገጥሟችሁ ያውቃል? ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን እና ሙሉ መጻሕፍትን ሳይቀር መሸምደድ የሚያደርግላችሁ ይህንን ነው። መልካም የመጽሐፍ ቅዱስ ወዳጆች ታማኝ የልብ ጓደኛ እና አማካሪ ሲሆኑ ታገኟቸዋላችሁ።

  1.  የእግዚአብሔር ቃል ይበልጥ የከበረ ስለሚሆንላችሁ ነው

ያለንን ነገር የበለጠ የምናፈስበት ነገር ለእኛ የበለጠ የከበረ ይሆናል። መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጥቂት ሰዓት የምታጠፉ ከሆነ ለእናንተ የከበረ እንዲሆን አትጠብቁ። ነገር ግን የክርስቶስ ቃል በውስጣችሁ በሙላት ይኖር ዘንድ ታላላቅ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን በልባችሁ ውስጥ በማጠራቀም ብዙ ሰዓቶችን የምታጠፉ ከሆነ፣ የዋናው ሕይወታችሁ የከበረ አካል ይሆናሉ (መዝሙር 119፥11ቈላስይስ 3፥16ዘዳግም 32፤47)።

  1.  የእግዚአብሔርን ክብር የበለጠ ስለምታዩ ነው

ከድርጊታቸው በመነሣት ስለ ሰዎች ልናውቅ የምንችለው ጥቂት ነገሮችን ብቻ ነው። በሚገባ ልናውቃቸው የምንችለው ከሚናገሩት ንግግር ነው። ተራሮች፣ ሕዋሳት፣ ጋላክሲዎች እያንዳንዳቸው ስለ እግዚአብሔር የሚሉት ነገር አላቸው። ይሁን እንጂ እግዚአብሔርን የእውነት ለማወቅ፣ ስለ እግዚአብሔር የከበሩ ነገሮችን ለማየት እና ለመደመም እርሱ ራሱ ስለ ራሱ የሚለውን ነገር በጥንቃቄ ልናደምጥ ያስፈልጋል። ምክንያቱም እግዚአብሔር በዋናነት ራሱን የሚገልጠው በቃሉ ውስጥ ነው (1 ሳሙኤል 3፥21)። ቃሉን መሸምደድ ድምፁን የበለጠ እንድንሰማ እና የበለጠ ክብሩን እንድንመለከት ያግዘናል።

  1.  ሽንገላን የመለየት አቅማችሁ እየጠራ ይመጣል

ዓለም ሁልጊዜ ትዋሻችኋለች። ዲያብሎስ የሐሰት አባት ነው (ዮሐንስ 8፥44)፤ ደግሞም ዓለም ሁሉ በእርሱ ኀይል ሥር ነው (1 ዮሐንስ 5፥19)። ኀጢአታዊ ባሕርያችሁ ይዋሻችኋል። ሐሰተኛ ወንድሞችም ይዋሽዋችኋል። የእግዚአብሔርን ቃል የበለጠ ባወቃችሁ ቁጥር እንዲህ ያሉ ነገሮችን እንዴት ማስተናገድ እንዳለባችሁ በማወቅ የተካናችሁ ትሆናላችሁ (2 ጢሞቴዎስ 2፥15)። ቃሉን በግልጽ በአእምሯችሁ ውስጥ በይበልጥ ስትይዙ የአጋንንትን ሽንገላ በመለየት ስኬታማ ትሆናላችሁ። ብዙ የእግዚአብሔር ቃል በአእምሯችሁ ውስጥ ሲኖር ሽንገላን የመለየት አቅማችሁ እየጠራ ይመጣል።

  1.  መከራ ስለሚገጥማችሁ ነው

መከራ በመንገዳችሁ ነው (ወይም ደርሶባችኋል)። መከራ ግራ የሚያጋባ እና አቅጣጫ የሚያስት ነገር ነው። እንዲህ ላሉ ወቅቶች የሸመደድናቸው ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በጣም ጠቃሚ ናቸው። ወደ አእምሯችሁ ከጉዳዩ ጋር የተያያዙ ጥቅሶች መምጣታቸው ብቻ ሳይሆን፣ በሕመም እና በፍርሀት ምክንያት ማስታወስ እንኳ ቢያቅታችሁ የት መሄድ እንዳለባችሁ ታውቃላችሁ። መጻሕፍትን መሸምደድ እነዚያን መጻሕፍት በአእምሯችሁ ላይ እንዲታተሙ ያደርጋል። ለመከራችሁ የሚናገሩ ምዕራፎች እና ክፍሎች የትኞቹ እንደ ሆኑ ታውቃላችሁ።

  1. ወንድሞቻችሁ እና እኅቶቻችሁ መከራ ስለሚገጥማቸው ነው

ይህ ነገር በመከራ ውስጥ እያለፉ ላሉ ወንድሞች ወይም እኅቶች የወንጌልን ማጽናናት እና ምክር ስናቀርብም ተመሳሳይ ነው። ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን መሸምደድ፣ እናንተን የሚጠቅም ብቻ ሳይሆን እምነትን የሚያጸና እውነት በጣም ባስፈለጋቸው ጊዜ ይህንኑ በማጋራት ሌሎችን የምንወድበት መንገድ ነው።

ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን የምንሸመድድበት መንገድ

መቃኘት፣ ማንበብ፣ በቃል ማለት፣ መደጋገገም

አንድ እና ሁለት ቁጥሮችን በመያዝ የምታደርጉት ሂደት ነው። እኔ እና ጆን ፓይፐር፣ እንዲሁም ሌሎች ብዙ ሰዎች አንድሩ ዴቪስ ያጎለበተውን በጣም ቀላል ስልት እንጠቀማለን። እንደ ምሳሌ ዮሐንስ 1፥1-3ን እንጠቀም።

[1] በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም ከእግዚአብሔር ጋር ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።

[2] እርሱም በመጀመሪያ ከእግዚአብሔር ጋር ነበረ።

[3] ሁሉ ነገር በእርሱ ተፈጥሯል፤ ከተፈጠረው ሁሉ ያለ እርሱ የተፈጠረ ምንም የለም።

ቀን 1

  • ዮሐንስ 1፥1ን 10 ጊዜ ማንበብ (እያንዳንዱን ጊዜ ስታነብቡ ቃላቱን በአእምሯችሁ ላይ ለማተም አንብቡ)
  • ከዚያም መጽሐፍ ቅዱሳችሁን ዝጉት እና ዐሥር ጊዜ ደጋግሙት (ድምፃችሁን ከፍ አድርጋችሁ እንድትደጋግሙት አበረታታችኋለሁ)

ቀን 2

  • ዮሐንስ 1፥1ን ከልሱ ከዚያም በቃላችሁ ዐሥር ጊዜ ደጋግሙት
  • ዮሐንስ 1፥2ን ዐሥር ጊዜ አንብቡ
  • መጽሐፍ ቅዱሳችሁን ዝጉትና ዐሥር ጊዜ ደጋግሙት

ቀን 3

  • ዮሐንስ 1፥1ን አንድ ጊዜ በቃላችሁ በሉ
  • ዮሐንስ 1፥2ን ዐሥር ጊዜ በቃላችሁ ደጋግሙ
  • ዮሐንስ 1፥3ን ዐሥር ጊዜ አንብቡ
  • መጽሐፍ ቅዱሳችሁን ዝጉትና ዐሥር ጊዜ ደጋግሙት

እንዲህ እያለ ይቀጥላል። መከለስ፣ ማንበብ፣ በቃል ማንበብ፣ መደጋገገም። አንድን ቁጥር በቃላችሁ በቀን አንዴ ለመቶ ቀን ብትደጋግሙ ለረጅም ጊዜ እንድታስታውሱት ሆኖ ይቀመጣል።

ይህን የመከለስ ልምድ ማዳበር እንዴት እንደምትችሉ ማወቅ ከፈለጋችሁ፣ አንድሩ ዴቪስ ይህንን እንዴት ማድረግ እንደምትችሉ የምታብራራ የ30 ገጽ መጽሐፍ አለችው።

ይህን ማሳካት ትችላላችሁ። ልታደርጉትም ይገባል። ረጃጅም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን መሸምደድ እንደምታስቡት ከባድ አይደለም። ከላይ በተጠቀሱት ምክንያቶች እና ሌሎች ምክንያቶች የተነሣ በሕይወታችሁ ልታደርጉት የምትችሉት ወሳኙ ነገር ነው። መቼም ቢሆን አይጸጽታችሁም።